
በእነ የተከበሩ ዮሃንስ ቧያሌው መዝገብ 16 ሰዎች ላይ አንድ ሰው ሕዳር 12 ከመጋረጃ በስተጀርባ ሆኖ ሊመሰክር ነው ፤ የተከሳሾች ጠበቆችም የምስክር ሂደቱን በመቃወም ጉዳዩን በይግባኝ እስከ ሰበር ሰሚ ችሎት ወስደውት ነበር።
(አውሎግሶን አንድነት- Awulogson Andinet ፣ ጥቅምት 18/2018 ፣ አዲስ አበባ- ኢትዮጵያ)
በእነ የተከበሩ ዮሃንስ ቧያሌው መዝገብ 16 ሰዎች ላይ አንድ ሰው ሕዳር 12/2018 በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ከመጋረጃ በስተጀርባ ሆኖ እንዲመሰክር በሚል ቀጠሮ ተይዞለታል።
አማራነታችን እንደ ወንጀል ተቆጥሮ ለአፈና ፣ ለእገታ ፣ ለስወራ በመጨረሻም ለእስር ተዳርገናል የሚሉት የፖለቲካ እና የሕሊና እስረኞቹ ምንም እንኳ የፈጠራ እና የማንነት ሽልማት ቢሆንምገዘ ከ15 ዓመት እስከ እድሜ እና ሞት የሚያስቀጣ የሽብር ክስ የተመሰረተብን በመሆኑ መመስከር ያለበት ከመጋረጃ በስተጀርባ ተደብቆ ሳይሆን በግልጽ ችሎት ሊሆን ይገባል ሲሉ ሂደቱን ተቃውመውታል።
“ይታያል በሩቁ” የሚል የፈጠራ ስም የተሰጠው ይህ የዐቃቤ ሕግ ምስክር በመጀመሪያውና ተሻሻለ በተባለው የሽብር ክስ ስሙ አልተካተተም ፤ ዐቃቤ ሕግ አሉኝ ካላቸው 21 ምስክሮች መካከልም 15 የሚሆኑ የፌደራል ፖሊስ እና የመከላከያ ሰራዊት አመራሮችንና አባላትን ካስመሰከረና ሂደቱን ከገመገመ በኋላ ክፍተቱን ለመሙላት ሲል አሰልጥኖ ያመጣው በመሆኑ ከመጋረጃ በስተ ጀርባ ተደብቆ ሊመሰክር አይገባም በማለት ተከራክረው ነበር።
ሌሎች ለከሳሽ የወገኑ ያሏቸውን ተደጋጋሚ የችሎት ክፍተቶችን በማካተትም ፍ/ቤቱ የኦህዴድ ብልጽግና አገዛዝ የፖለቲካ ፍላጎት ማስፈፀሚያ እየሆነ ነው ፤ በመሆኑም ይህ የፍትህ ሂደቱን የሚያዛባ አካሄድ እስካልታረመ ድረስ የሂደቱ አካል ሆነን ለመቀጠል ይቸግረናል በማለት ባለ 11 ነጥብ የአቋም መግለጫ ማውጣታቸውም ይታወሳል።
የተከሳሾች ጠበቆችም ምንም እንኳ በመጨረሻ ውሳኔውን ለማስቀልበስ ባይችሉም ቢያንስ ለታሪክ ይሆናል በሚል የተደብቆ ምስክር ሂደትን በመቃወም እስከ ሰበር ሰሚ ችሎት ሄደው መድከማቸው ግልጽ ታውቋል።
ጠቅላይም ሆነ ሰበር ሰሚ ችሎት የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት እንደወሰነው ለደህንነቱ ሲባል በመጋረጃ ተደብቆ ይመስክርባቸው በማለት በመወሰናቸው ነው ለሕዳር 12/2018 ቀጠሮ የተያዘው።
ይህ ቀጠሮ የተሰጠውም ተከሳሾች ጥቅምት 18/2018 በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ችሎት መቅረባቸውን ተከትሎ ነው።
በእለቱም የቂሊንጦ ማ/ቤት ኃላፊዎች በተለይም በፖለቲካ እና የሕሊና እስረኞች ፣ ቤተሰቦችና ጠበቆች ላይ በፍተሻ ስም ማንነትን እና ሰብአዊ ክብርን እየጣሱ ነው ፤ በማንነት እየተሳደቡ ነው ፣ የተከሳሾችንና የጠበቆችን ሰነድ እየነጠቁ ነው ፣ ከጠበቆችና ከቤተሰቦች ጋር ግንኙነት እየከለከሉ ነው ፣ እስረኛን ከመደብደብ እና ከማንገላታት አልፈው ሕክምና ጭምር እየከለከሉ ነው በሚል ለቀረበ ክስ የግቢው ጥበቃ እና ደህንነት ኃላፊ መሆናቸውን የገለጹ ኢ/ር ድሪባ ሰንበታ ቀርበው አብዛኛውን ክስ በማስተባበል ምላሽ ሰጥተዋል።
ተከሳሾች እና ጠበቆችም እድሉ ስለተሰጣቸው ደርሷል ያሉትን ግፍ እና በደል ሁሉ በዝርዝር አስረድተዋል።
ችሎቱም ጉዳዩን መርምሮ ተገቢ ነው ያለውን ትዕዛዝ ለመስጠት በሚል ለጥቅምት 26/2018 ቀጠሮ ስለመያዙ ለአውሎግሶን አንድነት የደረሰው መረጃ አመልክቷል ፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ተጨማሪ ዝርዝር መረጃ የምናጋራ ይሆናል።









You must be logged in to post a comment.